ሠላም ጤና ይስጥልኝ ክቡራን አንባቢያን ፤ ከዚህ መካነ-ድር (ድረ ገፅ) ላይ የምትወስዱትን ማንኛውንም ፅሑፍም ይሁን ምስሎች ለአዘጋጆቹ እና ለፀሐፊዎቹ ክብር ሲባል በምትጠቀሙበት ቦታ ሁሉ ምንጩን ትጠቅሱልን ዘንድ በትህትና እናሳስባለን ፡፡

Sunday, August 7, 2011

እንደገና


ገጣሚ፡ ገብረ ክርስቶስ ደስታ


ይናፍቀኝ ነበር …………
ዞሮ ዞሮ ከቤት
ይላል የኛ ተረት፡፡
አቧራው ፀሐዩ ይናፍቀኝ ነበር፤
አፈሩ ጠጠሩ ይናፍቀኝ ነበር፡፡
የመንደር ጭስ ማታ ………….
ይናፍቀኝ ነበር የሣር ቤት ጥቀርሻው
መደቡ ምሰሶው፤
ማገሩ ግድግዳው፤ አጥሩና ጥሻው፡፡
የፈራረሰ ካብ …………
ቀጭን ጠባብ መንገድ በመንደር የሚሮጥ
ቅጠል የሸፈነው፤
ሣር ያለባበሰው፤
እነዚህ፤ እነዚህ፤ ይናፍቁኝ ነበር፡፡ 

የተቆላ ቡና፤
የሚወቀጥ ቡና፤
የጎረቤት ቡና አቦል ሁለተኛ፤
የተረጨ ቆሎ የሚያርቅ መጋኛ፤
የሚጨሰው ዕጣን ……….
እንጀራ በመሶብ ወጥ የፈሰሰበት
ያገልግል እንጀራ የሚቧጠጥ ፍትፍት፤
የክክ ወጥ የሽሮ፤
የሥጋ የዶሮ፡፡
ይናፍቀኝ ነበር ቅራሪ ጉሽ ጠላ
ይናፍቀኝ ነበር ፊልተር ዞማ ኮላ፡፡
ያገራችን ድግስ ………
ከበሮ ጭፈራው፤
ዝላዩ እስክስታው፤ ስካሩ ሁካታው፡፡
ትርክምክሙ ነበር ግፊያው ትንቅንቁ
ኳኳታው እርግጫው ዘፈን ድብልቅልቁ፡፡
አሸወይና ወይና
እስቲ እንደ ጐጃሞች
አሲዮ ቤሌማ ……. ኦሆሆ አሀሀ
የቄስ ትምህርት ቤት
የሕፃናቱ ድምፅ፤
.. .. .. .. “ዜማ ነበር የናፈቀኝ
የጽጌ ጭፈራ ነበር የናፈቀኝ፡፡
ከበሮ ጸናጽል፤
ሆሣዕና ጥምቀት፤
ፋሲካ ገና ሁዳዴና ስግደት፤
ቡሄ ሆያ ሆዬ፤
የእስላሞች አረፋ የጋላ ሽጐዬ፤
የቁልቢው ገብርኤል፤
ልደታ፤
ፍልሰታ፡፡

ዕንቁጣጣሽ ነበር መስከረም ሲጠባ፤
አውቆ የበቀለ ወፍ ዘራሽ አበባ፡፡
ለምለም አረንጓዴ ………
ያልተጠበቀ መስክ ከብት የሚግጥበት፤
የደመና ግላጭ የሚጫወትበት፡፡
ሌላም ብዙ ነበር ……….
ሌላም ……. ደግሞ ሌላ፡፡
ያገሬ ሰው ነበር እኔን የናፈቀኝ፤
ጠይም ቆዳ ነበር እኔን የናፈቀኝ፤
ቀይ ዳማ ነበረ ጥቁር ቆዳ ነበር፤
ቁርንጫጭ ከርዳዳ፤ ዞማ ጠጉር ነበር፡፡
ያገራችን ቋንቋ ……
ያገሬ ሙዚቃ ያገራችን ዜማ
ጥበብ እጀጠባብ ያገራችን ሸማ፡፡
ነበረ ናፍቆቴ ለሁሉም …….
ለሁሉ፡፡
ለሸዋ፤ ለወሎ፤ ለትግሬ በጌምድር፤
ለጐጃም ወለጋ አሩሲ ኢሉባቡር፤
ኤርትራ ገሙ ጐፋ፤
ለሲዳሞ ከፋ፡፡
ለሁሉም ለሁሉ ነበረ ናፍቆቴ
አለብኝ ትዝታ
ዘመዶቼ ሳሙኝ፤
ጓደኞቼም ጋብዙኝ፤
ሊስትሮ ጨብጠኝ፡፡
ባለጋሪ ንዳ መንደሩን አሳየኝ
ያገሬ ልጅ ቆንጆቤት ለንግዳበዪኝ፡፡
አለብኝ ትዝታ …..
አዲስ አበባ ላይ ነበረ ናፍቆቴ
መናገሻ ነበር፤ እንጦጦ ነበረ፤
ኤረር ጋራ ነበር፤ ዝቋላ ነበረ፤
ጃን ሜዳ ነበረ፤ ኮተቤ ነበረ፤
ገፈርሣ ነበረ፤ ጉለሌ ነበረ፡
አዲሱ ከተማ …….
መርካቶ ዲጂኖ ችምችም ያለው መንደር
የከተማው እንብርት ደጃች ውቤ ሠፈር
የቸርችል ጐዳና፤
የባቡሩ ጣቢያ፤
ቢሾፍቱ ነበረ፤ ናዝሬት፤ ሞጆ፤ አዋሽ፡፡
ድሬዳዋ ነበር፤
ዓለም ማያ ነበር፡፡
ሐረርጌ ነበረ የተወለድኩበት
እናትና አባቴን ጥዬ የሔድኩበት፡፡
የሚካኤል ጓሮ ..…..
ሐረርጌ ነበረ፡፡
ዞሮ ዞሮ ከቤት ……..
አገሬ ነበረ እኔን የናፈቀኝ፡፡
ኢትዩጵያ ነበረች፡፡

4 comments:

  1. Yamiral yamiral yamiratYamiral yamiral yamirat

    ReplyDelete
  2. Dear bro, i have gone through your post with a mixed feeling,okay, let me not say anything, but i think good to be conscious that there are subjects never compromised, that you shall not do harm to others that you would not love others to do unto you, an ever golden principle.just know before you post. and don't allow/invite others to bombard you with criticisms on matters you are not a professional.

    ReplyDelete
  3. እንደዚ አይነት ታላላቅ ባለቅኔዎችን በጉጉት እንጠብቃለን አሁንም ያሉትን ይባርክልን አይንፈገን ስላከፈልከን አመሰግናለሁ ጥሩ ጅምር ነው ብስሬ

    ReplyDelete