ሠላም ጤና ይስጥልኝ ክቡራን አንባቢያን ፤ ከዚህ መካነ-ድር (ድረ ገፅ) ላይ የምትወስዱትን ማንኛውንም ፅሑፍም ይሁን ምስሎች ለአዘጋጆቹ እና ለፀሐፊዎቹ ክብር ሲባል በምትጠቀሙበት ቦታ ሁሉ ምንጩን ትጠቅሱልን ዘንድ በትህትና እናሳስባለን ፡፡

Monday, September 9, 2013

አንተ ነህ መስከረም

                                                            በገብረክርስቶስ ደስታ

ማለቂያ በሌለው ደማቅ ሰማያዊ፣
ከሩቅ ያለው ጋራ ተነክሮ ሐምራዊ፡፡
በዚያ ላይ ደመናው እንደ ጥጥ ተነድፎ፣
እየተራራቀ ሲያንጃብብ ተቃቅፎ፡፡
አንተ ነህ መስከረም፣
የሐምሌን ጨለማ የነሐሴን ዝናም፣
የሻርከው አንተ ነህ፣
በብርሃን ውበትህ፡፡
በክረምቱ ወራት ሰማዩን ያስጌጠው፣
የማርያም መቀነት በቀለም ያበደው፡፡
ጤዛው አርሶታል መሬቱ ላይ ለቆ፣
በቀይና ብጫ መስኩ ተለቅልቆ፡፡
ወንዝና ጅረቱ ድንጋይና አፈሩ፣
ሀገሩ ውብ ሆኗል ሜዳው ሸንተረሩ፡፡
ዕንቁጣጣሽ አንተ ስጦታህ የበዛ፣
ለሰው መታሰቢያ ውበት የምትገዛ፡፡


በሽቱ መዓዛህ ለውጠው ዓመቱን፣
ይታደስ ያረጀው ፍጥረት ሌላ ይሁን፡፡
ከምረው ዘመኑን ካበው ባመት ባመት፣
በወሩ ደረጃ ፍጥረት ይጓዝበት፡፡
ፍየሎች ይዝለሉ ቅጠል ይበጥሱ፣
ከተሰደዱበት ወፎች ይመለሱ፡፡
ይልቀሙት አህሉን፣ ይስሩ ቤታቸውን፣
ይስፈሩበት ዛፉን፣
የደስደስ ያሰሙ ንቦች ይራኮቱ፣
ይንጠራሩ አበቦች ይንቁ ይከፈቱ፡፡
አንበሳና ግልገል በመስኩ ይፈንጩ፣
ከብቶች ሣሩን ይንጩ፡፡
ሕፃናት ይሩጡ  ይሳቁ ይንጫጩ፣
ዛፎች ይተንፍሱ፣ የነፋሱ ጠረን፣
ይሰራጭ በቦታው ያውደው አገሩን፡፡

ዓደይ አበባ ነህ የመስቀል ደመራ፣
ጠረንህ አልባብ ነው አየርህ የጠራ፡፡
ያገር ልብስ አንተ ነህ ነጭ እንደበረዶ፣
ሰው የሚያጌጥብህ ጥበብህን ወስዶ፡፡
ቡቃያ ነህ እሸት ጓሚያ የበሰለ፣
አረንጓዴ ልብስህ በጌጥ የተሳለ፡፡
ጥቁር አረንጓዴ፣ ብጫማ አረንጓዴ፣
ቀለም  !  ቀለም !  ቀለም !
የሚያስተካክልህ የሚያስንቅህ የለም፡፡
ኀዘን የምታርቅ የገነት ምሳሌ፡፡
ይታደል ወለላህ ጠጁ በብርሌ
ይስከር በደስታ ሕዝቡ ይሳሳቅ፣
ድምፁ እየተማታ ሙዚቃው ይፍለቅ፡፡
ዕንቁጣጣሽ ብለን እንስጥህ ሰላምታ፣
ይጭብጨብ ለዝናህ፣
ይጭብጨብ ለስራህ
ይጭብጨብ ለመልክህ
አንተ ነህ መስከረም፡፡
ዘመን የምታድስ አስጊጠህ በቀለም፡፡



5 comments:


  1. በዲ/ን ዳንኤል በኩል ገብቼ ሁልጊዜም የምከታተልህ፣ግን ደግሞ ጽፌልህ የማላውቅ ተከታታይህ ነኝ ቃለ ህይዎት ያሰማልን፡፡ ዘመኑንን የመልካም ሥራ ውጤት ማስመዝገቢያ ያድርግልህ/ን/ !!

    ReplyDelete
  2. if I am not mistaken the orginal poem says embosana gilgel bemesku... not anbesana gilgel. >(

    ReplyDelete
  3. and in the last part you missed one full line - bichama arenguade, nitsuh arenguade, yater arenguade yemil.... sorry but i really like the poem and it is painful to see the mistakes

    ReplyDelete
  4. the poetry has so many mistakes

    ReplyDelete