ሠላም ጤና ይስጥልኝ ክቡራን አንባቢያን ፤ ከዚህ መካነ-ድር (ድረ ገፅ) ላይ የምትወስዱትን ማንኛውንም ፅሑፍም ይሁን ምስሎች ለአዘጋጆቹ እና ለፀሐፊዎቹ ክብር ሲባል በምትጠቀሙበት ቦታ ሁሉ ምንጩን ትጠቅሱልን ዘንድ በትህትና እናሳስባለን ፡፡

Tuesday, September 17, 2013

“ከሠማይ የወረደው” መስቀል

ፀሐፊ፡አለማየሁ አንበሴ 
ምንጭ፡አዲስ አድማስ ጋዜጣ / መስከረም 4 ቀን 2006 . እትም

ከሌሊቱ 9 ሰዓት በቅድሰት ክርስቶስ ሠምራ ነዓለ ንግስ ላይ በምዕመናን መካከል ተገልፆ በቀስተ ደመና ብርሃን በመብረቅ ድምፅ የወረደው መስቀል
ምስል፡-አዲስ አድማስ ጋዜጣ

                               ወደ አቃቂ ከተማ ከሚያስገባው ዋና የአስፓልት መንገድ በስተግራ 10 ኪሎ ሜትር ርቀት ገላን ጉራ በሚባለው ስፍራ የዛሬ 5 አመት የተቋቋመው የገብርኤል ቤተክርስቲያን ውስጥ ነሐሴ 23 ቀን የክርስቶስ ሰምራ በአለ ንግስ እየተከበረ እያለ ከሌሊቱ 9 ሰዓት የተከሰተው ግርግር ነው የዚህ ሁሉ መነሻ፡፡ ከባድ የፍንዳታ ድምጽ የሰሙ እና የቀስተ ደመና ቀለማትን የተላበሰ ብርሃን የተመለከቱ ነገሩን ከዝናባማው የአየሩ ሁኔታ ጋር በማያያዝ ብዙም ትኩረት አልሰጡትም ነበር የሚሉት የቤ/ክርስትያኑ መጋቢ፤ በነጎድጓድና በኢትዮጵያ ባንዲራ ቀለማት የታጀበ መስቀል ከሠማይ ሲወርድ አይቻለሁ ብለዋል፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ባሉት ቀናት መስቀሉን ለማየት ወደ ቤተክርስትያኗ የሚጐርፉ ምዕመናን በርክተዋል፡፡
ባለፈው ሃሙስ ከአቃቂ ከተማ በማለዳ ተነስተን 2 ሠአታት የእግር ጉዞ በኋላ ከቤተ ክርስቲያኑ ስንደርስ፣ በጥቂት ምዕመናን ተሣታፊነት የእለቱ ቅዳሴ እየተከናወነ ነበረ፡፡ ከቆይታ በኋላ ግቢው ከየአቅጣጫው የመስቀሉን ታሪክ ሠምተው በመጡ ምዕመናን ተሞላ፤ መስቀሉ ከሰማይ ሲወርድ አይቻለሁ የሚሉት መጋቢ ሃዲስ ፍስሃ፣ ስለ መስቀሉ አወራረድ ገለፃ ማድረግ የጀመሩት ከቅዳሴው በኋላ ነው፡፡
ግቢው ውስጥ ከቤተ ክርስቲያኑ ህንፃ አጠገብ መስቀሉ የወደቀበትን ስፍራ እያመለከቱ ይናገራሉ -ቦታው በቆርቆሮ ታጥሮ ድንኳን ተተክሎበታል። መስቀሉ አርፎበታል ከተባለው ስፍራ አፈር እየቆነጠረ የሚቀርብላቸው ምዕመናን አፈር እየተመለከቱ የመጋቢ ሃዲስን ገለፃ ያዳምጣሉ፡፡ 


ለቅድስት ክርስቶስ ሠምራ በአል ነሐሴ 23 ቀን የፀሎት ስርአት ከምሽቱ አምስት ሠአት አካባቢ እንደተጀመረ የሚያስታውሱት መጋቢ ሃዲስ፣ ከእኩለ ሌሊት ጀምሮ አካባቢው በቀስተደመና ብርሃን ደምቆ እንደነበር ይናገራሉ፡፡ የቤተክርስቲያኒቱ አገልጋዮችና ምዕመናን ለዚህ ልዩ ክስተት ብዙም ትኩረት አልሰጡትም፤ ከዝናባማው የአየር ፀባይ ጋር በማዛመድ አቅልለው ነው የተመለከቱት ብለዋል መጋቢ ሃዲስ፡፡ የቀስተ ደመናው ብርሃን አንዴ ሲደምቅ፣ አንዴ ሲደበዝዝ መቆየቱን መጋቢ ሃዲስ ጠቅሰው፣ ከሌሊቱ 9 ሠአት ንፋስ ለማግኘት በካህናት መውጫ በር በኩል ስወጣ ግን ደብዛዛ የነበረው ብርሃን የበለጠ ደምቆ፣ እንደቀን ብርሃን ወገግ ብሎ ታየኝ ብለዋል፡፡
አሻቅቤ ስመለከት ሠማዩ በነጭ ደመና ተከቦ ተመለከትኩ፡፡ አፍታም አልቆምየ፤ በኢትዮጵያ ባንዲራ ቀለማት የተጠቀለለ አንዳች ነገር በዝግታ ከሠማይ እየተገለባበጠ ሲወርድ አየሁ ይላሉ መጋቢ ሃዲስ፡፡
ከቤተክርስቲያኑ ቤተልሄም አጠገብ ያለውን የአገር አቋራጭ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ መስመር ተሸካሚ ማማ እያመለከቱ፣ “ከሠማይ እየተጠቀለለ የሚወርደው ነገር ከማማው አካባቢ ሲደርስ ነጐድጓዳማ ድምፅ ማሠማት ጀመረ የሚሉት መጋቢ ሀዲስ፤ “መሬት ላይ ሲያርፍ በከፍተኛ የፍንዳታ ድምፅ አካባቢውን የእሣት ንዳድ በመሰሉ ብርሃን ሞላው ይላሉ፡፡ “ቤተልሄሙ ተቃጠለ እያልኩ ብጮህም ድምፄን የሰማ ሰው አልነበረም፤ ለደቂቃዎች ያህል ለሠዎች እንዳይሠማ ሆኖ ታፍኖ ነበር የሚሉት መጋቢ ሀዲስ፤ “ድምፄ መሰማት ሲችል ግን  ካህናቱ ጩኸቱን ሰምተው ተደናግጠው ወደ ውጭ መጡ ብለዋል፡፡ አንዳች አደጋ ደርሶ እሳት ተቀጣጥሎ ሊሆን ይችላል በሚል ድንጋጤ ሁሉም እሣቱን ለማጥፋት እንደተሯሯጠ ጠቅሰው፣ ነገር ግን በአካባቢው ከብርሃን በቀር የእሣት ቃጠሎ ማግኘት አልተቻለም ብለዋል - መጋቢው፡፡

መስቀሉን ከወደቀበት ለማንሳት የሞከረ አንድ የቤተክርስቲያናችን ወጣት አገልጋይ ወጣት ተስፈንጥሮ በወደቀበት 4 ቀን ራሱን እንደሳተ የሚናገሩ የቤተክርስትያኑ አገልጋይ፣ ከምሽቱ 9 ሰዓት ከፍንዳታ ጋር አካባቢው በብርሃን ተሞልቶ ስናይ የእሳት ቃጠሎ መስሎን ነበር ብለዋል፡፡ይህ የቤተክርስቲያናችን ወጣት አገልጋይ ወደ ደመቀው ብርሃን ተጠግቶ ለማየት ሞከረ፡፡ አንዳች ነገር ወደ ላይ አስፈጥንሮ መሬት ላይ ጣለው፡፡ ምዕመናን ተደናገጡ፡፡ የኤሌትሪክ መስመር ተበጥሶ ኮንታክት ፈጥሮ ይሆናል የሚል ጥርጣሬ ነበር ያደረብን ሲሉም ተርከዋል፡፡የወደቀው ወጣት ምላሱ ተጐልጉሎ በወደቀበት ራሱን ስቶ ተዘርግቷል የሚሉት መጋቢ ፍሰሃ፤ ከወደቀበት በጥንቃቄ አንስተን ፀበልና ቅባ ቅዱስ ብናደርግበትም አልተሻለውም ብለዋል፡፡ ከዚያ በኋላ ነው ካህናቱ እንደምንም ወደ ብርሃኑ አካባቢ ተጠግተው የተመለከቱት፡፡ እናም በብርሃን የታጀበ መስቀል መሬት ላይ ወድቆ አዩ ብለዋል መጋቢው፡፡ ካህናቱና ምዕመናኑ በአግራሞት ሲመለከቱ ቢቆዩም የእሣቱ ወላፈን ይፋጃል ያሉት መጋቢ ፍሰሃ፤ በርቀት መጐናፀፊያ ተወርውሮበት እንዲለብስ እንደተደረገ ይገልፃሉ፡፡ የተቋረጠው ስርዓተ ማህሌት 10 ሰዓት በኋላ እንደቀጠለ የተናገሩት መጋቢ ፍሰሃ፣ በካህናቱ ትዕዛዝ ጠዋት 1230 ላይ መስቀል በወረደበት ቦታ ላይ ድንኳን ተተከለ፤ ብፁዐን አባቶችም በስልክ እንዲያውቁ ተደረገ ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ በማግስቱ የአቡነ ተክለሃይማኖት ክብረ በል ስለነበረ ብዙዎቹ ጻጳሳት ወደ ደብረሊባኖስ፣ ቀሪዎቹም ወደየአድባራቱ ሄደው ስለነበረ መምጣት አልቻሉም ብለዋል - መጋቢው፡፡ ከበላይ አካላት በተነገረን መሠረት ለወረዳው ፖሊስ ካሳወቅን በኋላ፣ የፖሊስ ሃይል አካባቢውን ተቆጣጠረ የሚሉት መጋቢ ሃዲስ፤ ቅዳሜ እለት የማህበረ ቅዱሳን አባላት መጥተው መመልከታቸውን ገልፀዋል፡፡ በዚያው እለት ከሰአት በኋላ ለመምጣት ቀጠሮ የሰጡ ጳጳሳት ግን ከአንድ ሰአት በላይ በረዶ የቀላቀለ ዝናብ በመጣሉና ጭቃው የማያስገባ በመሆኑ ከመንገድ ተመልሰዋል። በማግስቱ እሁድም አክራሪነትን በመቃወም ሰልፍ የሚካሄድበት ቀን በመሆኑ መምጣት አልቻሉም፡፡ ሰኞ እለት ነሐሴ 27 ቀን ግን በርካታ ጳጳሳት በቦታው ተገኝተው በበርካታ ምዕመናን ታጅቦ መስቀሉ ከወደቀበት መሬት ተነስቶ፣ ወደ መቅደሱ እንዲገባ መደረጉን መጋቢ ፍሰሃ ተናግረዋል፡፡ በደረሰበት አደጋ ራሱን ስቶ የቆየው ወጣት፤ 4ኛው ቀን መንቃቱንና በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኝ መጋቢ ሃዲስ ጠቅሰዋል፡፡ 
እያንፀባረቀ በሃይለኛ ግለት ያቃጥል ነበር የተባለው መስቀል፤ በማህበረ ቅዱሳን መሪዎችና በጳጳሳት የተጐበኘ ሲሆን የኢየሱስን ስቅለት የሚያሳይ ወርቃማ ቅርጽ ያለው ነው፡፡ 

መስቀሉ ከወረደበት ቦታ በሊቃነ ጳጳሳት ከተነሳ በኋላምስል፡-አዲስ አድማስ ጋዜጣ
ወጣቱ ሲጠየቅም፣ መስቀሉን ተመልክቶ ሊያነሳው እጁን ሲሰነዝር ከኋላው አንዳች ህፃን ልጅ የመሰለ ነገር ጐትቶ መሬት ላይ እንደጣለውና ከዚያ በኋላ የሆነውን እንደማያውቅ መግለፁን እኚሁ መጋቢ ተናግረዋል፡፡
መስቀሉ ከወደቀበት መሬት ተነስቶ ሲገባ ከፍተኛ ግለት እንደነበረውና የተሸከሙት አባት “እያቃጠለኝ ነው ሲሉ እንደነበር መጋቢ ፍሰሃ ገልፀዋል፡፡ መስቀሉ የሰው ስራ እንዳይሆን የተጠራጠሩ ካህናት መኖራቸውን ያመኑት መጋቢ ፍሰሃ፣ መስቀሉ ከምን እንደመጣ የሚያውቀው ፈጣሪ ነው ብለዋል፡፡ 
አቶ እንግዳው የተባሉ የአካባቢው ነዋሪ፣ መስቀሉ ከሠማይ ሲወርድ እንዳልተመለከቱ ጠቅሰው፤ በጳጳሣቱ ተነስቶ ወደ መቅደሡ ሲገባ ወርቃማ ብርሃን ነበረው ብለዋል፡፡ አንዳንድ የአካባቢው ሠዎችም ሌሊቱን ነጐድጓዳማ ድምፅ መስማታቸውንና በማግስቱም ይህን ክስተት በቤተክርስቲያኑ ከነበሩ ሰዎች ታሪኩ እንደተነገራቸው ገልፀዋል፡፡ ለአካባቢው ፀጥታ በማሰብ መስቀሉ በየእለቱ ለምዕመናን እንዳይታይ ከቤተክህነት ትዕዛዝ እንደተላለፈ ጠቅሰው፤ መስከረም 19ቀን 2006 . በቤተክርስቲያኑ ቅፅር ግቢ መስቀሉን በይፋ ለእይታ ለማብቃት ቀጠሮ መያዙን መጋቢ ሃዲስ ተናግረዋል፡፡

************************************************************************************
መስቀሉ ሁለት ሳምንት በኋላ ለህዝብ እይታ እንደሚቀርብ ታውቋል፡፡  

ፀሐፊ፡አለማየሁ አንበሴ 
ምንጭ፡አዲስ አድማስ ጋዜጣ / መስከረም 4 ቀን 2006 . እትም

7 comments:

  1. LE EGZIHABHER YEMISANEW MINIM YELEM

    ReplyDelete
  2. enameseginalen

    ReplyDelete
  3. This a land of mythology and a mythic society. We Ethiopians have not completed our evolution, b/c we are still taking such claims as facts. It is better for 'God' to send Bread rather than 'Cross'. ,,,, Start thinking my people!

    ReplyDelete
  4. This has proved to be untrue; it is one of the business projects by Tehadsos.Don't believe it

    ReplyDelete
  5. Enate Ethiopia Holy Land!!!

    ReplyDelete
  6. ye egziabhar sera naw

    ReplyDelete