ሠላም ጤና ይስጥልኝ ክቡራን አንባቢያን ፤ ከዚህ መካነ-ድር (ድረ ገፅ) ላይ የምትወስዱትን ማንኛውንም ፅሑፍም ይሁን ምስሎች ለአዘጋጆቹ እና ለፀሐፊዎቹ ክብር ሲባል በምትጠቀሙበት ቦታ ሁሉ ምንጩን ትጠቅሱልን ዘንድ በትህትና እናሳስባለን ፡፡

Sunday, April 12, 2015

‹‹ጎልጎታ››፡- ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር...!!!

በዲ/ን ክንፈ ገብርኤል

                 ፍቅረ ብእሲት ወወይን ሞተ ናቡቴ፣                            
        ወለኦርዮን ቅትለቱ፡፡                            
  ሞተ ወልድሰ የዋህ፣                           
እንበለ ክልኤሆን በከንቱ፡፡                                
      እንበለ ክልኤሆን ሞተ፣ ከመ ኢንበል ባሕቱ፡፡                          
ቤተ እስራኤል ኅሩይ ዓፀደ ወይኑ፣
ወቤተ ክርስቲያን መርዓቱ፡፡
(ዕዝል ክብር ይእቲ ቅኔ ዘአለቃ ተክለ ጽዮን-ዘዋሸራ) *የዚህን ቅኔ ትርጉም በጽሑፍ ውስጥ ያገኙታል፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንትና መምህራን እንደሚሉት ቅኔ በጥንታዊቷ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለምስጋናና ለውዳሴ የሚውል ጥልቅ ምስጢርና ትርጓሜ ያለው ሰማያዊ ጥበብ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት በሞት የተለየን የኢትዮጵያ ወዳጅ የሆነው፣ እውቁ የማኅበረሰብ ሳይንስ ምሁር አሜሪካዊው ፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን Wax and Gold በሚለው መጽሐፉ:- ‹‹ቅኔ ለኢትዮጵያ ረቂቅ መንፈሳዊ ባሕሏ ነው፡፡›› ሲል አስተያየቱንና አድናቆቱን አስፍሮ ነበር፡፡

     በዚሁ የሀገራችን ሀብትና ሕያው ቅርስ በሆነው ቅኔ አባቶቻችን ጥልቅ የሆነ ምስጢርን ከትውልድ ወደ ትውልድ አስተላልፈውልናል፡፡ በዚህም መሠረት የጌታን ስቅለት፣ መከራውን፣ ሞቱንና ትንሣኤውን በምናስብበትና በምናከብርበት በዚህ ወቅት፣ ከላይ በጠቀስነው በአለቃ ተክለ ጽዮን ቅኔ ውስጥ ልብን በሚመስጥ ሁኔታ የክርስቶስ ኢየሱስ ሕማምና ሞት በብሉይ ኪዳን ዘመን ከነበሩት ሁለት ሰዎች የአሟሟት ምክንያት ጋር ተነጻጽሮ የቀረበበት ቅኔያዊ ምስጢር በእጅጉ የሚደንቅ፣ ውበቱና ምሥጢሩ ነፍስ ድረስ ዘልቆ የሚሰማ፣ አጥንትንና ጅማትን ሁሉ የሚሰረስር ነው፡፡

    እንደ ብሉይ ኪዳን መጻሕፍት እስራኤላዊው ናቡቴ የአባቶቼ ርስት የሆነውን የወይን ቦታውን አልሰጥም፣ እምቢኝ አሻፈረኝ በማለቱ በኤልዛቤል ምክርና ውሳኔ በግፍ ተገድሎ ደሙ በከንቱ እንዲፈስ ሆኗል፡፡ ሌላኛው በዚህ ቅኔ ውስጥ የተገለጸው እስራኤላዊው አርበኛ ኦርዮን፣ ንጉሥ ዳዊት በሚስቱ ላይ በፈጸመው ዝሙት ምክንያት ይህንን ኃጢአቱን ለመሸፈን ሲል በወሰደው እርምጃ ከሚስቱ የተነሳ በንጉሥ ቀጭን ትዕዛዝ የሞት ደብዳቤውን ይዞ በመሔድ በግፍ ለሞት እንዲዳረግ ሆኗል፡፡

        ነገር ግን ይሉናል አለቃ ተክለ ጽዮን በቅኔያቸው፡- የየዋህ ወልድ (የእግዚአብሔር ልጅ) ሞት ግን ከእነዚህ ከሁለቱ ይለያል፡፡ የእርሱ ሞት ለተመረጡ የወይን ግንድ ለሆኑት ለርስቱ፣ ለቤተ እስራኤልና ሙሽራው ለምትሆን ለቤተ ክርስቲያን ወይም ለእኛ ለምእመናን እንጂ፤ በማለት ለሁሉ ድንቅ የሆነውን የኢየሱስ ክርስቶስን ሕማም፣ መከራ፣ ሞት፣ የቀራኒዮውን ውለታ፣ ፍጹም የሆነውን የእግዚአብሔርን ዘላለማዊ ፍቅር እንዲህ በሚደንቅና በሚጥም የቅኔ መንፈሳዊ ውበት ገልጸውታል፡፡

በዛሬው መጣጥፌ በክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት የሚከበረውን የስቅለትንና የትንሣኤን በዓል በተመለከተ ለዚህ መጣጥፌ የመረጥኩት የዕውቁ ሠዓሊና ባለ ቅኔ የገብረ ክርስቶስ ደስታን ‹‹ጎልጎታ›› በሚል ርዕስ የተጠበበትን የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የሥነ ስቅለት አስደናቂና ዘመን አይሽሬ (classical) ሥራውን ነው፡፡ የዚህን ገጣሚና ሠዓሊ፣ እጅግ ተወዳጅና ተደናቂው የሆነውን ‹‹የጎልጎታን›› ፍቅርን ተጠበበትን እጅግ ድንቅ ሥራውን ፅንሰትና ውልደት ታሪክና እንዲሁም ስለ አምላክ ዘላለማዊ ፍቅሩ በአጭሩ ላወጋችኹ ወደድኹ፡፡
ገጣሚና ሠዓሊ ገብረ ክርስቶስ ደስታ በኢትዮጵያ ዘመናዊ ሥነ ጥበብ ታሪክ ውስጥ ስሙ ጎልቶ ከሚጠቀሱ የጥበብ ሰዎች ዘንድ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀስ እውቅና ታላቅ ሰው ነው፡፡ ገ/ክርስቶስ ዘመናዊ የሥዕል ሙያን በአገር ውስጥና በአውሮፓ ከተማረ በኋላ በአገሩ እምብዛም አልቆየም ነበር፡፡ በአገራችን በተከሰተው የ1966ቱ አብዮት፣ ከነደደው የነውጥና የለውጥ እሳት የተነሣ እንደ ብዙዎቹ ኢትዮጵያውያን ምሁራንና ወገኖቹ የእርሱም ዕጣ ፈንታ ስደት ሆኖ ነበር፡፡
ገ/ክርስቶስ በትምህርትና በስደት ሕይወት ለረጅም ዓመታት በባሕረ ማዶ በቆየባቸው ጊዜያት ውስጥ አውሮፓውያኑ ወይም በአጠቃላይ ነጮች ለአፍሪካውያንና ለጥቁር ሕዝቦች የሚያሳዩት ዘረኝነት፣ ያላቸው ንቀትና ጥላቻ በእጅጉ ያብሰለስለውና እረፍት ይነሳው ነበር፡፡
ከምንም በላይ ደግሞ የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ምድር ተምሳሌት፣ በዓለማችን ታሪክ ታይቶና፣ ተሰምቶ በማይታወቅ ጀግንነትና ወኔ ኢትዮጵያውያን አባቶቹ ወራሪውን የኢጣሊያንን ቅኝ ገዢ ኃይል በዓድዋ ጦር ግንባር በአኩሪ ጀግንነት አሳፍረው የመለሱ ኃያላን መሆናቸውን አሳምሮ ለሚያውቀው ገ/ክርስቶስ ይህ የአውሮፓውኑ ትምክህትና ንቀት ከመገረምም በላይ ሆኖበት ነበር፡፡
በዚህ የአገሩ ታሪክም በእጅጉ የሚኮራውና በዓለም ታሪክ አንጸባራቂ የሆነ የጥቁር ሕዝቦችን ነጻነት ድል፣ ፋና ወጊን ታሪክ በደማቸው ከጻፉ፣ የነጻነት ምድር ከሆነችው ከኢትዮጵያ ለተሰደደው፣ ለነጻነቱና ለክብሩ ቀናዒ ለሆነው ገ/ክርስቶስ ደስታ አውሮፓውያኑ በጥቁሮች ወገኖቹ ላይ ያንጸባርቁት የነበረው ንቀትና ጥላቻ ፈጽሞ ሊቀበለው የማይችልና ሊቋቋመው ያቃተው ፈታኝ ገጠመኙ ነበር፡፡
አውሮፓውያኑ ዘንድ ‹‹ጥቁር በምንም ዓይነት ከነጮች ጋር በእኩልነት እንዲመደብ የሚያስችለው ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊም ሆነ ፖለቲካዊ ስብእና የለውም፡፡›› በሚለው እሳቤያቸው ከአፍሪካ የጀግኖች ምድር ከሆነችው ከኢትዮጵያ ለሄደው ገ/ክርስቶስ ከፍተኛ የሆነ ሥነ ልቦናዊ ጫና አሳድሮበት ነበር፡፡ ከዛም አልፎ ‹‹አምላክ ነጭ ወይም አውሮፓዊ›› እንደሆነ በድፍረት በሚሰብኩበት በዛ በባዕድ ምድር፣ ያ የጥበብ ምርኮኛ ኢትዮጵያዊ በእጅጉ ልቡ ተነክቶ፣ ነፍሱም ክፉኛ አዝናበት ነበር፡፡
እናም ይህ የጥቁር ምድር አፈር ትሩፋት የሆነው ጥበበኛው ገ/ክርስቶስ ከእኛ በላይ ክርስቲያን ለአሣር በሚሉትና ይህን የአውሮፓውያኑን መርዘኛ የሆነ ዘረኛ አስተሳሰብና ምልከታ፣ ጥልቅና ምጡቅ በሆነ የጥበብ ሥራው ሊሞግታቸው፣ ሊያሳፍራቸው ከነፍሱና ከመንፈሱ ጋር ተማከረ፡፡
ከልጅነቱ ጀምሮ ከታወቁት የቅኔ መምህርና የተዋሕዶ ሊቅ ከሆኑት ከአባቱ ከአለቃ ደስታ ነገዎ ዘንድ ፊደል ቆጥሮ፣ ዳዊት ደግሞ፣ ዜማ ተምሮ፣ በዘመኑ የነበሩትን የአባቱን ዘመነኞች ሊቃውንት ቅኔና የመንፈሳዊን ዓለም ረቂቅ የሆነ ትንታኔና ትርጓሜ የሆነ ጥልቅ እውቀት ጠዋት ማታ እየሰማ ላደገው ለገ/ክርስቶስ፣ መንፈስ የሆነው እግዚአብሔር በምን መንገድ፣ በምን ጥበብ የአውሮፓዊነት ወይም የነጭነት ቆዳን ወይም መልክን እንደተጎናጸፈ ፈፅሞ ግራ ነበር ያጋባው፡፡
እናም ይህ እውቀት የሥጋ፣ ይኽ ድንቁርናም ከክፉው፣ የዚህ ጥበባቸው ምንጩም የሐሰት አባት ዲያቢሎስ መሆኑን ሊነግራቸው ሠዓሊው ቀለሙን በጠበጠ፣ ብሩሹን ወደረ፣ ሸራውንም ወጠረ፡፡ የአውሮፓውያኑን የዘርኝነት እኩይ አስተሳሰብ፣ ከሰው ዘር አልፎ እግዚአብሔርን ሳይቀር እንኳን ነጭና ዘረኛ ያደረጉበትን ከንቱ የሆነውን ትምክህታቸውንና ድንቁርናቸውን የእንቧይ ካብ ሊያደርገውና እውነቱን ሊነግራቸው ቆርጦ ገ/ክርስቶስ ቀለሙን ከሸራው አዋኻደ፡፡
እናም ጥበበኛው በሥዕሉ ዓለምን ያስደመመ ድንቅ የፍቅርን ቅኔን በብሩሹ ተቀኘ፡፡ ባለ ቅኔውና ሰዓሊው ገ/ክርስቶስ ይህን ‹‹ጎልጎታ›› ብሎ የሰየመውን ቆዳ አምላኪዎቹን፣ አውሮፓውያኑን ራሳቸውን እንኳን ሣይቀር በእጅጉ ያስደመመውን ይህን ታላቁን የጥበብ ሥራውን ከብርቱ ቅናት፣ ከፍቅርና ከእውነት በመነጨ የእውቀት ብርሃን ተነሳስቶ ነበር ፍቅርን በብሩሹ ከሸራው ጋር ያዋኻደው፡፡ በዚህም ድንቅ የጥበብ ሥራው ገ/ክርስቶስ አውሮፓውያኑን ቆዳ አምላኪዎችን፣ ዘረኞችና ትምክህተኞችን እንዲህ ሲል በጥበብ ሥራው ሞገታቸው፣ አሳፈራቸውም፡-

እናንተ እናመልከዋለን የምትሉት እግዚአብሔር ግን ነጭም ጥቁር ወይም ቢጫም አይደለም፡፡ አፍሪካዊም አውሮፓዊም ወይም አሜሪካዊ አይደለም፡፡ እርሱ የሁሉ ፈጣሪ፣ የጥበብ ሁሉ መዝገብ፣ የፍቅር ምንጭ የሆነ- የፍቅር አምላክ ነው!! እናም እርሱን የዘር፣ የጎሳ፣ የነገድ፣ የቋንቋ፣ የቆዳ የቀለም ድንበር ፈፅሞ የማይለየው፣ የማይገድበው ሁለተናው ፍቅር የሆነ፣ በፍቅር የተጥለቀለቀ፣ በፍቅር ስለ ፍቅር የቆሰለ፣ በፍቅር ስለ ፍቅር በደም የተነከረ፣ ደም ግባቱና ውበቱ ደም የጎረፈበት፣ በደም የተረጨ፣ በደም የታተመ፣ በደም የተጥለቀለቀ፣ ሞትን በሞት የረታ ሕያው፣ ዘላለማዊ ፍ-ቅ-ር ነው!!

ይህ ተአምረኛ የሆነው የገ/ክርስቶስ ‹‹ጎልጎታ›› የጥበብ ሥራው፡- የሕማም ሰው፣ እንወደው ዘንድ ደምግባት የሌለውን፣ የተናቀውን፣ ስለ ሰው ልጆች ሁሉ መተላለፍ ቆሰለውን፣ ስለ በደላችንም የደቀቀውን፣ ስለ እኛ ብርቱ ሕመምን የታመመውን፣ በጌቴሰማኒ የደም ላብ ያላበውን፣ ስለ ሰው ልጆች ኃጢአት የተጨነቀውን፣ በጎልጎታ፣ በቀራኒዮ አደባባይ የተቸነከረውን፣ ክርስቶስ ኢየሱስን በደም ገለጸው፡፡

የእሾኽ አክሊልን የደፋው ራሱ፣ በሚስማር የተቸነከሩት ቅዱሳን እጆቹና እግሮቹ፣ በጦር የተዋጋው ጎኑ፣ በሮማውያኑ ጅራፍ የተተለተለው ጀርባውና የቆሰለው መላው አካላቱ፣ ፍቅርንና ምሕረትን በደም ጅረት፣ ለሰው ልጆች ሁሉ የሚያውጁ፣ ዘላለማዊ የሆኑ የፍቅር ሕያው ማህተሞች መሆናቸውን በይፋ ገለጸላቸው፡፡

እርሱ ኢየሱስ መቼም መቼም የማይደበዝዝ፣ የማይነጥፍ፣ የማይደርቅ ሕያው የፍቅር ደም ጅረት፣ የዘላለም ሕይወት ምንጭ፣ የደም መሥዋዕት፣ ረቂቅ ውበትን የተጎናጸፈ ቅዱስ መሥዋዕት መሆኑን ጠቢቡ በብሩሹ በቀይ ቀለም፣ በደም ቋንቋ ገለጸልን፣ ተቀኘልንም፡፡

የዚህ ትንግርተኛ የጥበብ ሰው የገ/ክርስቶስ ዘመን አይሽሬ ሥራው ይህ ፍቅር ዘር፣ ጎሳ፣ ቀለም፣ ዜግነት ሳይል ሁሉንም በእኩልነት የሚያፈቅር እንጂ እናንተ እንደምታስቡት አምላክ ነጭ፣ ፈጣሪ አውሮፓዊ ወይም አሜሪካዊ አሊያም አፍሪካዊ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ፍቅር፣ ፍቅርም እግዚአብሔር ነው እንጂ፡፡ ‹‹በጎልጎታ›› ድንቅ የጥበብ ሥራው ገብሬ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ፣ የቅድስት ድንግል ማርያም ልጅ  የሁሉ ሰው ወዳጅ፣ በደም የታታመ፣ በደም የተዋበ፣ ፍጹም ፍ-ቅ-ር፣ ሕያው ፍ-ቅ-ር፣ በፍቅር ስለ ፍቅር የተሠዋ የመሥዋዕት በግ ነው እንጂ፤

ሲል ገ/ክርስቶስ ይህን የእግዚአብሔር ልጅ የሆነውን የኢየሱስ ክርስቶስን የቀራኒዮውን ፍቅሩን ‹‹ጎልጎታ›› ብሎ በሰየመው የጥበብ ሥራው በደም ቀለም፣ በደም ጎርፍ፣ በደም ብሩሽ ፅልመት በዋጠው በመሰለው ሸራው ላይ በብሩሹ ፍቅርን በደም ጎርፍ፣ ፍቅርን በደም ቅኔ እንዲህ ተጠበበት፣ እንዲህ ተደመመበት፣ እንዲህ ተቀኘበት ቃል ሊገልጸው በማይችል ልዩ ውበት፣ ልዩ ጥበብ!!
‹‹ጎልጎታ›› የገብረ ክርስቶስ ዘመን አይሽሬ (Classical) የሆነች በብዙዎች ነፍስ፣ አጥንትና ጅማት ድረስ ዘልቃ፣ የፍቅርን ብርቱ፣ ኃይልና ጽናት የምትገልጽ ሥራው እንደሆነች በርካታ አድናቂዎቹ ይመሰክራሉ፡፡ በአንድ ወቅትም የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ ጥናት መጽሔት (Ethiopian Studies Journal) ላይ የገ/ክርስቶስ የጥበብ ልጁና የሙያው ባልደረባ የሆነው አቶ እሸቱ ጥሩነህ ስለ ገብሬ ታሪክና ስለ ‹‹ጎልጎታ›› ድንቅዬ የጥበበብ ሥራው ባቀረበው የጥናት ጽሑፉ እንዲህ ነበር ያለው፡-
…ይህ የገ/ክርስቶስ ደስታ ‹ጎልጎታ›› ብሎ የሰየመው የሥነ ሥቅለት ሥዕላዊ ድርሰት የፍቅርን፣ የመሥዋዕትነትን፣ የቤዛነትን፣ የሕያውነትና የዘላለማዊነትን፣ እንዲሁም የነጻነትንና ሰላምን ምንነት ባጫሩ በሕብረ ቀለማት የቃኘበትና የተቀኘበት ነው፡፡ መስቀሉ እውነታዊ ነው፡፡ የተሰቀለው ክርስቶስ ግን ተምሳሌታዊ ነው፡፡ ሥዕሉ እስከተሠራበት እስከዚያን ጊዜ ድረስ ብዙ ሠዓሊዎች አካሉን ወይም ስጋውን አልፎም እውነታዊ ምስሉን ከነሥቃዩ ይሥላሉ እንጂ፣ እንደ ገብረ ክርስቶስ ክቡር ደሙን፣ ንጹሕ መሥዋዕትነቱን በቀይ ሕብረ ቀለም ብቻ ተምሳሌት አድርገውና ወሰነው የሠሩ የሉም…፡፡
ይህን በሚመለከት ይላል አቶ እሸቱ ጥሩነህ፣ ‹‹የገብረ ክርስቶስ ደስታ፣ አጭር ትውስታና ጨረፍታዊ ዕይታ›› በሚል ርዕስ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ባቀረበው በዚሁ ጥናቱ፣ ይህን በሚመለከት የጀርመን አገር ጓደኛው የነበረው ዶ/ር እጓለ ገብረ ዮሐንስ እንዲህ በማለት ጽፏል ይለናል፡-

ሠዓሊ ተብሎ የጎልጎታን ተራራ ያልወጣ፣ የቀራኒዮን ትልቁን ትራጀዲ ያላየ የለም፤ ግን የገብረ ክርስቶስ ሥነ-ሥቅለት ለብቻው ነው፡፡ ቀለም ተናጋሪው ነው፣ የሚታየው ንጹሕ ደም ብቻ ነው፡፡ ግራና ቀኝ የነበሩት (የተሰቀሉት) እነ ፋይታዊ ቦታ የላቸውም ተዘንግተዋል፡፡ ወይም ሠዓሊው ሊያያቸው አልፈለገም፣ ይገርማል፡፡ ጥበብ ከንጹሕነት ከጽርየት ከርቀት ብቻ እንጂ ከሌላ ጋር ግንኙነት የሌላት መሆኑን ለመረዳት ይቻላል፡፡

ዛሬም ድረስ የገ/ክርስቶስ የፍቅር የነፍሱ ምጥ ውልደት የሆነችው ‹‹ጎልጎታ›› የፍቅር ሕያው መዝገብ፣ የጥበብ ሥራዎቹ ሁሉ ቁንጮ ሥራ ሆና በዚህ ክብሯ፣ ማዕረጓና ሕያውነቷ ዘልቃለች፡፡ ፍቅርን በመሥዋዕትነት፣ ፍቅርን በእውነት፣ ፍቅርን በደም እየተረከች፣ በደም እየሞሸረች፣ በእሾኽ አክሊል፣ በደም እያነገሠች፣ በጦርና በችንካር በደም እያስዋበች፣ በደም እየተረከች…፡፡
ይህ የገ/ክርስቶስ ዘመን አይሽሬ የሆነ የጥበብ ሥራው ለበርካታ ዓመታት በስደት ከቆየበት ከወደ አውሮፓ መጥቶ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በጀርመን መንግሥት እርዳታ በስሙ በተቋቋመው የሥነ ጥበብ መዘክር ውስጥ ይገኛል፡፡ ገና ወደዚህ ቤተ መዘክሩ አዳራሽ ውስጥ ስትገቡ ዓይናችሁ ፊት ለፊት በሚታየው በዚህ ትንግርተኛ የገብሬ ጥበብ ሥራ ‹‹ጎልጎታ›› ላይ ዓይናችሁ ተተከሎ ይቀራል፡፡ በዛ ፅልመት በዋጠው በሚመስለው ሸራ ላይ በተረጨው ደም ውስጥ የሰው ልጆች ሁሉ የመውደቅና የመነሳት ታሪክ፣ ጅማሬና ፍፃሜው በደም ቋንቋ፣ በደም ቀለም፣ በደም ብሩሽ በጉልህ ደምቆ ይታያል፡፡
ያን መሳጭ፣ ያን ምሥጢረኛ፣ ያን ትንግርተኛ፣ ያን ነፍስን፣ አጥንትንና ጅማትን ዘልቆ በሚመትር ልዩ ኃይልንና ጥበብን በተቸረው በገብሬ ‹‹በጎልጎታ›› ድንቅ የጥበብ ሥራ ላይ መላ አካላታችን ለቅጽበት ዓይን ሆኖ ፈዞ፣ ደንግዞና ተውጦ ይቀራል፡፡ እናም ከቤተልሔም ግርግም እስከ ጎልጎታ-ቀራኒዮ የፍቅር ኃይል፣ የፍቅር ቤዛነት፣ የፍቅር ጥበብ፣ የፍቅር ትሕትና፣ የፍቅር ትዕግሥት፣ የፍቅር ጽናት፣ የፍቅር ኤልሻዳይነት፣ የፍቅር ሕያውነት… ቃላት ሊገልጹት በማይቻላቸው በደም ቋንቋ፣ በደም ቀለም ፍቅርን ያሳያችኋል፡፡ ፍቅር በለሆሳስ፣ መንፈሳዊ በሆነ ሰማያዊ ቋንቋ ያናግረችኋል፣ ያወራችኋል፡፡

በዚህ በእጅጉ አስገራሚ፣ አስደናቂና አስደማሚ በሆነው የጥበብ ሥራው ገ/ክርስቶስ ፍ-ቅ-ር-ን በጥበብ ቋንቋ፣ በረቂቅ ክህሎት፣ ልዩ በሆነ ኃይል ትላንትና፣ ዛሬ፣ ነገም እስከ ዘላለምም ሲያውጅ ታዩታላችኹ፣ ትሰሙታላችኹ ሊያውም በለሆሳስ በሆነ የነፍስ ጩኸት፣ የነፍስ ድምፅ፣ የነፍስ ቋንቋ!! በገ/ክርስቶስ በ‹‹ጎልጎታ››ሥራ ላይ ይህን ታላቅ እውነት፣ ይህን በደም የተከፈለ፣ በደም የጸና የፈጣሪ፣ የአምላክ ፍቅር፣ ምሕረት፣ ይቅርታ፣ በጎነት፣ በረከት፣ ቸርነት፣ ርኅራኄ፣ ፍትሕ፣ ፍርድና ጽድቅ በደም ቋንቋ፣ በደም ቅኔ ይነበባል፣ በጉልህ ይተረጎማል፡፡
ለዚህም ነው በፋሲካው፣ በትንሣኤው ሌሊት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ካህናት አባቶችና ሊቃውንቱ በማሕሌታቸው፡-‹‹ወምድርኒ ትገብር ፈሲካ፣ ታኀፂባ በደም ክርስቶስ፡፡››/‹‹ምድር ንፁሕ የፍቅር መሥዋዕት በሆነው በክርስቶስ ኢየሱስ ክቡር ደም ታጥባ በሐሴትና በደሰታ ፋሲካን ታክብር፡፡›› እያሉ ይህን ታላቅ የፍቅር፣ የምስራች ሰማያዊ ዜማ ለምድሪቱና ለፍጥረት ሁሉ በታላቅ ድምፅ ደግመው ደጋግመው በታላቅ ድምፅ የሚያሰሙት፣ የሚያበስሩት፡፡

ፍቅርንና ሰላምን የተሞላ የስቅለትና የፋሲካ በዓልን ለሕዝበ ክርስቲያን ሁሉ በመመኘት ልሰናበት!
ሰላም!


1 comment:

  1. Please when Kidane Mihret (filseta )is coming explen about that
    why we are fast for 15 days`.Thank you

    ReplyDelete